Tuesday 30 July 2013

ETVዬ፤ ይሄኛው መንገድ የት ያደርሰ ይሆን!? አቤ ቶክቻው!!

አንድነት ፓርቲ ፤

“የፀረ ሽብር ህጉ ከሀገሪቱ ህገ መንግስት ጋር የሚፃረር በመሆኑ” ሊሰረዝ ይገባዋል አሉ፡፡

የኢቲቪው ጋዜጠኛ፤

ተቃዋሚዎች የሽብርተኞች ህግ ይሰረዝ እና ሀገራችን በሽብረኞች ትሞላ እንደ ሴሪያ እና እንደ ግብጽ ትበጣበጥ ይላሉ… እርስዎ በዚህ ላይ ምን የሚሰጡን አስተያየት አለ…?


አስተያየት ሰጪ፤

(ድንግጥ ብለው) “እንዴ… እንዴት እንደዚህ ይላሉ ነውር አይደለም አንዴ… መበጣበጥ ለማን ይጠቅማል… ይሄ ከአንድ ሀገር ሊመራ ካሰበ የፖለቲካ ፓርቲ አይጠበቅም…”

ድምፃችን ይሰማዎች፤

“የሼክ ኑሩ ግድያ የተቀነባበረ ድራማ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ተቃውሟችንን የምናሰማው ፍፁም ሰላማዊ በሆነ መንገድ ነው፡፡ የምንሞትለት እንጂ የምንገድልበት ሀይማኖት የለንም፤ ስለዚህ የሼሁ ግድያ መንግስት ነው የፈፀመው” ሲሉ ይከሳሉ…

የኢቲቪ ጋዜጠኛ፤

ፅንፈኞቹ የሼህ ኑሩ ግድያ ድራማ ነው እንጂ አልሞቱም ይላሉ እርስዎ ይሄንን እንዴት ያዩታል…?

አስተያየት ሰጪ፤

(ግራ ተጋብተው) “እንዴ… እንዴት እንደዚህ ይባላል… ይሄ ጭካኔ ነው፡፡ ለእነርሱ ድራማ ቢመስላቸውም እኛ ግን የቀበርነው አባት ነው፡፡”

አንድነት ፓርቲ፤

“የህገ ወጥ የሰዎች ዝውውርን ለመግታት ደላሎችን ማሰር ብቻ መፍትሄ አይሆንም ስር ነቀል የፖሊሲ ማሻሻያ ማድረግ ያስፈልጋል” አለ፡፡

የኢቲቪ ጋዜጠኛ፤

ተቃዋሚዎች በቅርቡ በህገወጥ የሰዎች ዝውውር ላይ ተሳታፊ የሆኑ ደላሎች መታሰራቸውን እንቃወማለን ብለዋል፡፡ እርስዎ በዚህ ላይ ምን የሚሰጡን አስተያየት አለ…?

አስተያየት ሰጪው፤

(ተደንቀው) “ይገርማል… እንግዲህ የህገ ወጥ ዝውውር ደላሎቹ ራሳቸው ናቸው ማለት ነዋ… ሰው እንዴት ወንጀለኛ አይታሰር ይላል… ወገኖቻችን ለከፋ አደጋ እየተጋለጡ ደላሎቹ አይታሰሩብን ካሉ ራሳቸውም ወንጀለኞች ናቸው ማለት ነው”

በጁምዓው ተቃውሞ፤

አንድ ሰውዬ ያረጀ ባንዲራ ይዞ ታየ፡፡ ልብ አድርጉልኝ አንድ ሰውዬ ነው፡፡ ሰውዬው ምናልባትም በቤቱ ያገኛትን አሮጌ ባንዲራ ይዞ ወጥቷል ወይ ደግሞ…. (ወይ ደግሞውን እንተወው… ብቻ ግን አንድ ሰውዬ ብቻ ነው ይሄ ሰውዬ በፍፁም ሚሊዮኖቹን ሊወክል አይቻለውም፤ ተቃውሞ ስፍር ቁጥር የሌላቸው ሰዎች የተሳተፉበት ነው)

የኢቲቪው ጋዜጠኛ፤

አክራሪ ሀይሎች ባለፈው አርብ ባንዲራውን ሲቀዳድዱ ነበር ይሄ የሀገር ክህደት አይደለም ይላሉ…

አስተያየት ሰጪ፤

እንዴ የሀገራቸውን ባንዲራ መቅደድማ አይገባም… ኢትዮጵያ እኮ ሀገራቸው ናት…ነውር አይደለም እንዴ…

ሌላም ሌላም…

ልብ አድርጉልኝ ኢቲቪ ይሄንን ድራማ የሚሰራው ሊዝናናን አይደለም፡፡ የምሩን ነው፡፡ ኮስተር ብሎ ነው፡፡ እየቀለደ አስደለም እየቀለደብን ነው እንጂ…

እና የምሬን ልጠይቅ ETVዬ፤ ይሄኛው መንገድ ግን የት ድረስ ያስኬድ ይሆን!?

No comments:

Post a Comment