Friday 14 December 2012

የታህሣሥ ግርግር :-

የታህሳስ 5 1953 መፈንቅለ መንግስት
ፎቶ:- መስከረም 1953ዓ/ም
ከግራ ወደ ቀኝ ጄነራል መንግስቱ ነዋይ ሻምበል አበበ ቢቂላ ጄነራል መርዕድ አበበ
 ምክንያት:- ጨቋኙን የፊውዳሉን አገዛዝ አስወግዶ ህገ መንግስታዊ ተራማጅ ዘውዳዊ ስርዓት መዘርጋት
መንስኤ:-ንጉሰ ነገስቱ በመጀመሪያ ወደ ምዕራብ አፍሪካ ቀጥሎም ብራዚልን ለመጎብኘት ከሀገር መውጣት
ድርጊቱ የተከናወነበት ሰዓት:- ታህሳስ 5 1953 ጠዋት የለውጥ ፈላጊ ናቸው የሚባሉትን ልዑል ራስ እምሩ ኃይለ ሥላሴ ን በጠቅላይ ሚኒስትርነት መሾማቸውንና ይፋ አደረጉ።

የመፈንቅለ መንግስቱ መሪ ተዋንያን:- ብ/ጄ/ል መንግስቱ ነዋይ፣ ተራማጅ ምሁሩ ግርማሜ ንዋይ፣ የህዝብ ደህንነት ሹሙ ኮ/ል ወርቅነህ ገበየሁ የፖሊስ ሰራዊት ዋና አዛዥ ብ/ጄ ጽጌ ዲቡ
ስኬት:- የንጉሱን ቤተሰቦችና ከፍተኛ ባለስልጣናት በእጃቸው አስገብተዋል፣ ከፍተኛ የሆነ ዲስኩርና የመንግስት ለውጥ መደረጉን በራዲዮ ለህዝቡ አሰማ(አልጋ ወራሹ አስፋ ወሰን መልዕክት “…ድንቁርናን ከመካከላቸው አጥፍተው በአእምሯቸው መራቀቅና በኑሮ ደረጃው እየገፉ የሚሄዱ የዓለም ሕዝቦች ላይ የኢትዮጵያን ሕዝብ ሊያደርሰው የሚችል የማይፈጸም የቃል ተስፋ መስማት ሳይሆን እውነተኛ ተግባር ላይ የዋለ የሕዝብ የአእምሮና የኑሮ እድገት የሀገር ኃብት ልማት ፕሮግራም እስከዛሬ ድረስ ተዘርግቶ ካለማየቱም በላይ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ነጻነታቸውን ያገኙ የአፍሪቃ አገሮች እንኳን ሳይቀሩ በሚፈጽሙት የስልጣኔ እርምጃዎች የኢትዮጵያን ሕዝብ እየቀደሙና ወደኋላ እየጣሉ ወደፊት የሚገሰግሱ መሆናቸው ለኢትዮጵያ ዕለት በዕለት ገሃድ እየሆነለት ሄደ። ይሄም ሁኔታ ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ የኢትዮጵያን ሕዝብ የረጅም ተስፋ መጨረሻ ላይ አላደረሰውም። ይህም ከመሆኑ የተነሳ ከጥቂት ጊዜ ወዲህ የተጀመረው የሕዝብ እንቅስቃሴ እነሆ ዛሬ ሥልጣንን ጨብጦ ለኢትዮጵያ ሕዝብና ለሀገሪቱም መድኅን ከመሆን ደረጃ ላይ መድረሱን ለኢትዮጵያ ሕዝብ ልገልጽላችሁ ዕድል በማግኘቴ ደስታዬ ፍጹም ነው።…….”)፣የራዲዮ ጣቢያ፣ ብሔራዊ ባንክ የገንዘብ ሚኒስተርና በመዲናዋ ቁልፍ ቁልፍ ቦታዎችን ተቆጣጥረ
መፈንቅለ መንግስቱን ለማክሸፍ በዋናነት የተንቀሳቀሱ:- ጄ/ል ከበደ ገብሬ፣ ምድር ጦር አዛዡ ጄ/ል መርዕድ መንገሻ፣ ደጃዝማች አስራተ መድህን ካሳና ሌሎች ለንጉስ ታማኝ የጦር አባላት
 
የከሸፈበት ቀን:- ታህሳስ 7 1953
 
የከሸፈበት ምክንያት:- በቂ ዝግጅት ማጣት፣ የህንዝላልነት የተሞላበት አካሄድ (ለምሳሌ ለንጉሱ ታማኝ የነበሩ የጦር መኮንኖችን በቁጥጥር ስር አልተደረጉም)፣ የፓትሪያርኩ ውግዘት(የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ አቡነ ባስልዮስ
“ክርስቲያን የሆናችሁ ልጆቼ እንዲሁም የመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ…..ትናንትና አንዳንድ የክብር ዘበኛ ሠራዊት አባላት….ሀገራቸውን ክደዋል።….እነኚህን ከሃዲዎች አትመኑ አትከተሏቸው። በተሰጠኝ ሥልጣን አውግዣችኋለሁ…”)፣ የህዝቡ ዝቅተኛ ንቃተ-ህሌና
 
ውጤት:- የመፈንቅለ መንግስቱን መሪዎችን፣ የንጉሱን ቤተሰቦችና ከፍተኛ ባለስልጣናት እና ሌሎችን ጨምሮ ወደ 250 የሚሆኑ ሰዎች ሞት፣ ጦርና ፖሊስ ሰራዊቱ ላይ ብቁ መሪዎችን እጦት፣ የንጉሰ ነገስቱ አይነኬነት ለመጀመሪያ ጊዜ መቃወም እንደሚቻል አሳይቷል፣ ከኋላ ለመጡ እምቢታዎችና የለውጥ እንቅስቃሴ መንገድ ጠርጓል፣ የንጉሱን ጭካኔና ጥርጣሬ ጨምሯል<<የዓድመኞቹ ዓላማ መንግሥቱን ገልብጠው አንድ መንግሥት ለማቋቋም፣ አልጋ ወራሻችንን ምክንያት አድርጎ ለመስበክ የተቻላቸውን ያህል በብዙ መንገድ ሠርተዋል። ግን ዓላማው የሚበልጠው የነሱን አምቢሲዮን መሙላት፣ የቀረውን የሕዝቡን ያታለሉበት ነገር ሁሉ እኛ ከፈራነው ነገር የወጣ አንድም ነገር የለም።>>
 
ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ፣ ከግርግሩ ክሽፈት በኋላ ለውጭ ጋዜጠኞች ከሰጡት ቃለ ምልልስ።
ፍፃሜ:- ታኅሣሥ 15ቀን ጽጌ ዲቡ ከጦር ሠራዊት ኃይሎች ጋር ሲታኮሱ ቀደም ብለው ሲሞቱ፣ ኮሎኔል ወርቅነህ ደግሞ በተከበቡ ጊዜ “እጄን አልሰጥም ብለው” ራሳቸውን አጠፉ። መንግሥቱና ገርማሜ ግን በቤተ መንግሥቱ ጋራዥ በኩል ሾልከው ወደ ቀጨኔ መድሃኔ ዓለም በኩል ጫካ ለጫካ ኮበለሉ። ወንድማማቾቹና ባልደረባቸው ሻምበል ባየ ጥላሁን ከአዲስ አበባ ድሬ ጨለባ በሚባል ሥፍራ ወደ ሚገኝ የዘመዳቸው እርስት በማምራት ላይ ሳሉ ነው የተከበቡት። እዚሁ ሥፍራ በተደረገው የተኩስ ልውውጥ ሻምበል ባየ እና ገርማሜ ሲገደሉ መንግሥቱ ነዋይ ግን ክፉኛ ቆስለው ይያዛሉ። የሁለቱ ሟቾች አስከሬን አዲስ አበባ ቤተ መንግሥቱ ደጃፍ ላይ ካደረ በኋላ በማግሥቱ ከኮሎኔል ወርቅነህ ገበየሁ አስከሬን ጋራ ምኒልክ አደባባይ ላይ ተሰቅሎ ዋለ። መንግሥቱ ንዋይ ቆስለው ከተያዙ በኋላ ከወር በላይ በህክምና ቆይተዋል። ከህክምናውም በኋላ የካቲት 3 ቀን ለፍርድ ሲቀረቡ አንድ ዓይናቸው ድሬ ጨለባ ላይ የጠፋ ከመሆኑም በላይ ሁለተኛውም አስተማማኝ አልነበረም፡፡

የፍርድ ውሣኔ:-ፍርድ ቤቱ መጋቢት 19ቀን ውሳኔውን ሰጠ። ጄነራሉ ይግባኝ ይሉ እንደሁ ሲጠየቁ ከዚህ የሚከተለውን እንደትንቢት የሚቆጠር ምላሽ ሰጡ።

”እናንተ ዳኞች! የበየናችሁብኝን የሞት ፍርድ ያለይግባኝ ተቀብያለሁ። ይግባኝ ብዬ የሚመለከትልኝ የኢትዮጵያ ሕዝብ ቢሆን ኖሮ ይግባኝ ማለት በፈልኩ ነበር። ነገር ግን ይህ እንደማይሆን አውቃለሁና የዓፄ ኃይለ ሥላሴን ፊትለማየት አልፈቅድም። በእግዚአብሔር ስም በተቀመጣችሁበት የፍርድ ወንበር ላይ ከመቀመጣችሁ በፊት በእኔ ላይ የምትሰጡትን ፍርድ ታውቁት እንደነበር ሳስበውና ፍርድ እስከዚህ መድረሱን ስታዘብ ኀዘኔ ይብሳል። ለኢትዮጵያ ሕዝብ አንድነት፣ ነጻነትና እርምጃ የተነሳሁ ወንጀለኛ ነኝ እንጂ ላፋጀው የተነሳሁ ወንበዴ አይደለሁም። ይህን ማድረግ ፈልጌ ቢሆን ኖሮ ማንም የማይወዳደረው ሠራዊትና መሣሪያ ሳላጣ ዛሬ ከእናንተ ፊት ለመቆም ባልበቃሁ ነበር። እኔ ከዓፄ ኃይለ ሥላሴ ድንክ ውሾች ያነሰ ደመወዝ የሚያገኙ ሁለት የተራ ወታደሮችን አጣልቼ ለማደባደብና ሀገር ለማፍረስ አለመነሳሳቴን የሚያረጋግጥልኝ ከእናንተ በትዕዛዝ ያገኘሁትን ፍርድ ለመቀበል እዚህ መቆሜ ነው። ከእኔ በፊት በግፍ የፈሰሰው ንፁህ የኢትዮጵያዊያን ደም ብዙ ነው፡፡ በዓፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት ግፍ ሽልማት በመሆኑ እኔ ለመሞት የመጀመሪያው ሰው አልሆንም፡፡ ሥልጣን አላፊ ነው፡፡ እናንተ ዛሬ ከጨበጣችሁት የበለጠ ሥልጣን ነበረኝ፡፡ ሀብትም አላጣሁም፡፡ ነገር ግን ሕዝብ የሚበደልበት ሥልጣንና ድሃ የማይካፈለው ሀብት ስላልፈለግሁ ሁሉንም ንቄ ተነሳሁ። አሁንም እሞታለሁ፡፡ ሰው ሞትን ይሸሻል ፡፡ እኔ ግን በደስታ ወደሞት እሄዳለሁ፡፡ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ታላቅነት ቀድመውኝ መስዋዕት የሆኑትን አብረውኝ ተነስተው የነበሩትን ጀግኖች ወንድሞቼን ለመገናኝት ናፍቄአለሁ፡፡

 የጀመርኩት ሥራ ቀላል አይደለም። ነገር ግን አልተሸነፍኩም። ወገኔ የሆነው የኢትዮጵያ ሕዝብ የጀመርኩትን ሥራ በቅርብ ጊዜ ውስጥ ፈጽሞ እራሱን እንደሚጠቅምበት አልጠራጠርም። ከሁሉ በበለጠ የሚያስደስተኝ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ልሠራለት ካሰብኳቸው ሥራዎች አንዱ የኢትዮጵያን ወታደር ዋጋና ክብር ከፍ ማድረግ ሲሆን ይህ ኀሳቤ ሕይወቴ ከማለፉ በፊት ሲፈፀም ማየቴ ነው፡፡ ዛሬ መኖራችሁን በማየቴ ነገ መሞታችሁን ረስታችሁ አሜን ብላችሁ ቀናችሁን በማስተላለፍ በመገደዳችሁ በእኔ ላይ ሳትፈርዱ በራሳችሁ ላይ የፈረዳችሁ መሆናችሁን አላስተዋላችሁም፡፡ እኔ የተነሳሁት ከትክክለኛ ህግና ከህሊናችሁ ውጭ ለመፍረድ እንዳትገደዱ ለማድረግ ነበር፡፡ ባጭሩ በእኔ ላይ ለመፍረድ የቸኮላችሁትን ያህል አሥር እና አሥራ አምስት ዓመት የምታጉላሉት የድሀውን ሕዝብ ጉዳይ እንደዚህ አፋጥናችሁ ብትሠሩትና ብትሸኙት ኖሮ የእኔ መነሳት ባላስፈለገ ነበር። ከእናንተ ከዳኞችና የሞት ፍርድ እንድትበይኑብኝ ካዘዛችሁ ሰው ይልቅ ፍርድ ተቀባይ የዛሬው ወንጀለኛ የነገው ባለታሪክ ነኝ። የኔ ከጓደኞቼ መካከል ለጊዜው በሕይወት መቆየትና ለእናንተ ፍርድ መብቃት የመመዘኑን ፍርድ ለመጭው ትውልድ የሚያሳይ ይሆናል፡፡ ዋ ! ዋ ! ዋ ! ለእናንተና ለገዢአችሁ፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ሃሳቤ በዝርዝር ገብቶት በአንድነት በሚነሳበት ጊዜ የሚወርድባችሁ መዓት አሰቃቂ ይሆናል፡፡ በተለይ የአፄ ኃ/ስላሴ የግፍ መንግስት ባላደራዎች ሆነው ድሀውን የኢትዮጵያ ህዝብ ሲገሸልጡት ከነበሩት መኮንን ሀ/ወልድና ገ/ወልድ እንግዳወርቅን ከመሳሰሉት በመንፈስ የታሰሩ በስጋ የኮሰሱ መዠገሮች መካከል ጥቂቶቹን ገለል ማድረጌን ሳስታውስና የተረፉትም ፍፃሜያቸውን በሚበድሉት በኢትዮጵያ ህዝብ እጅ ላይ መውደቅ ሲሰማኝ ደስ ይለኛል፡ ”
 
በዚሁም መሠረት ጄነራሉ መጋቢት 21ቀን 1953ዓ/ም በስቅላት ተቀጡ።

No comments:

Post a Comment