Thursday 13 June 2013

ጋዜጠኛ አለምነህ ዋሴ የቁንጅና ፈቃድ ቢሮ ሃላፊ


ፋሲል አ.

ሰሞኑን ቤቴልሄም አበራ(ቤቲ) የተባለች ወጣት ኢትዮጵያዊት በቢግ ብራዘር አፍሪካ  ትእይንት (show) ላይ ከሴራሊዮኑ ቦልት ጋር ፈጸመችው ስለተባለው ወሲብ በተለየዩ  ማህበራዊ ድረ-ገጾች እና መገናኛ ብዙሃን የሚሰጠው አስተያየት እንደቀጠለ ነው::በዚህ የቢግ ብራዘር ትእይንት ላይ ከዚህ በፊት በተደረጉ ውድድሮች ላይ የተለያዩ ጥንዶች እንደዚህ አይነት የወሲብ ድርጊት መፈጸማቸው የተዘገበ ሲሆን ይህ የቢግ ብራዘር ትእይንት በባህሪው ለእንደዚህ አይነት ድርጊቶች የተጋለጠ ለመሆኑ ከዚህ ቀደምም ሆነ አሁን የተደረጉት ድርጊቶች በቂ ማሳያ ናቸው :: 


ይህ እንዳለን ሆኖ  ቤቲ ፈጸመችው ለተባለው ድርጊት ብዙ ኢትዮጵያኖች በተለያዩ  ድረ ገጾች አዋረደችን” አሰደበችን” ምነው ባትሄድ ቢቀርባት ኖሮ “እና የመሳሰሉትን የተቃውሞ  አስተያየቶች እየሰጡ ሲሆን ከነዚህም አስተያየቶች አንዱ ታዋቂው ጋዜጠኛ አለምነህ ዋሴ በሬድዮ የሰጠውን አስተያየትም ተከታትዬው ነበር:: 


ጋዜጠኛ አለምነህ ዋሴ እንደጋዜጠኛ ሳይሆን እንደ ተጋባዥ እንግዳ ከሌላ ጋዜጠኛ የሚቀርብለትን ጥያቄዎች እየመለሰ በቀረበው በዚህ ፕሮግራም ላይ አለምነህ አስተያየቱን ሲጀምር በዚህ ቢግ ብራዘር አፍሪካ ትእይንት ላይ ከሌሎች የአፍሪካ  ሃገሮች የሚመጡት ተወዳዳሪዎች በሃገራቸው ታዋቂነት ያላቸው የቲቪ ሾው አዘጋጆች፣ አርቲስቶች ወይንም በሞያቸው ዝናን ያተረፉ ታዋቂ ሰዎች (celebrities)  ሲሆኑ ከእኛ ግን የሚወስዱት እኔ የማላውቃቸው ሰዎች ናቸው ( ለማለት የፈለገው በሞያቸው በህዝብ ዘንድ ታዋቂ ያልሆኑትን ለማለት ነው) ሲል የቢግ ብራዘርን አዘጋጆችን ይወቅሳል:: 


እንግዲህ እኔን እንደገባኝ ከቤቲ ይልቅ የሃገራችን ታዋቂ አርቲስቶች (celebrities )  ቢሄዱ ኖሮ  ይሻል ነበር ምናልባትም አንዋረድም ነበር ብንዋረድም ውርደቱ የጋራ  ይሆን ነበር ሲል ይገልጻል::ይገርማል በመጀመሪያ  ደረጃ የቢግ ብራዘር አዘጋጆች ከአንድ ሃገር ታዋቂ አርቲስትም ይምረጡ መደበኛ ኖርማል ሰው ያ የተመረጠው ግለሰብ ወደ ውድድሩ ከመግባቱ በፊት የውድድሩን ህግጋቶች ከማጥናቱም በተጨማሪ በግሉ ደግሞ እንዴት ማሸነፍ እንዳለበት የአቅሙን ዝግጅት አድርጎ የሚገባ ሲሆን በተጨማሪም ወደ ውድድሩ ከገባም በኋላ በውድድሩ ውስጥ በሚፈጠሩ የተለያዩ አጋጣሚዎች እራሱን እያስተካከለና እያዋሃደ የሚሄድበት ሲሆን የሸመደደውን ወይም ያጠናውን የሚያንበለብልበት መድረክ ሳይሆን ከሁኔታዎች ጋር የራሱን የግል ስብእና፣ ስሜትና አስተሳሰብ የሚያንጸባርቅበት ትእይንት በመሆኑ ተወዳዳሪው አርቲስት ይሁን ወታደር፣ ፖለቲከኛ ይሁን መምህር፣ ድንገት በሚፈጠሩ አጋጣሚዎች የሚመልሰው ( የሚወስነው) ግብረ መልስ (reaction )  እንደየሰው የውስጥ ስብእና፣ ልምድ፣ አስተሳሰብና  ውስጣዊ ጥንካሬ የሚለያይ እንጂ አርቲስት ስለሆነ ትክክለኛ ውሳኔዎችን ያስተላልፋል ሌላው ሰው ግን ሊከብደው ይችላል ብሎ ሙሉ በሙሉ  መደምደም ይከብዳል:: 


ሌላው አለምነህ ከዚሁ ጋር አያይዞ  የገለጸው ነገር የምናከብራቸው አርቲስቶች ወደ ውድድሩ ቢሄዱ ያስደስቱናል! ያኮሩናል! የሚፈጽሙትም ነውር ነገር ካለ አብረን ችግሩን እንቀበላለን ሲል ይገልጻል:: ወይ አለምነህ ታዲያ ቤቲስ ይህንን ድርጊት ባትፈጽምና ብታሸንፍ ኖሮ  ታስደስተን! ታኮራን! የለም እንዴ? እንዲሁም ያው ልክ አንተ እንዳልከው ነውር ነገር ካለም ያው ችግሩ የጋራ ይሆናል ማለት ነው ስለዚህ አብረን መቀበል የለብንም እንዴ ? ነው ወይስ ቢያኮሩንም ቢያሳፍሩንም አርቲስቶች ብቻ ናቸው መሄድ ያለባቸው እያልከን ነው? 


ቀደም ሲል አርቲስት ወደ ውድድሩ ተልኮ  ቢሆን ኖሮና  ነውርም ካለ አብረን እንቀበለዋለን ሲል የነበረው አለምነህ ቤቲ መምህርት ናት በመሆኑም ትልቁ የሚሰቀጥጠው ነገር ልጆቻችንን ወዴት ነው የምንልከው? ሲል የተምታታ  ስጋቱን ይገልጻል:: እንዴ ደግሞ ነውር የአርቲስትና የመምህር የሚባል ልዩነት አለው እንዴ ጋዜጠኛ አለምነህ? ልጆቻችን ትምህርት እና ስነ ምግባር የሚማሩት ት/ቤት ብቻ ነው እንዴ? በዲቪዲው በሲዲው የአርቲስቶቻችን ስራ በየቤታችን እየገባ አይደለም እንዴ? አርቲስትስ አንድን ጤናማ  ማህበረሰብ ለመቅረጽ ከፍተኛ ሚና  እንዳለው አልሰማህ ይሆን? 


የጋዜጠኛውና የአለምነህ ውይይት ሲቀጥል ጠያቂው ጋዜጠኛው ጥያቄ  መሰል አስተያየቱን በማስከተል ቤቲ ይህን ውድድር ካሸነፈች ወደ ሆሊውድ መሄድና የራሷን የጉዞና አስጎብኝ ድርጅት መክፈት እንደምትፈልግ ገልጻለች  በማለት ካብራራ በኋላ ቤቲ ወደ ሆሊውድ ከሄደችማ  ሌላ ነገር ነው ማለት ነው ሲል ቤቲ ወደ ሆሊውድ ሄዳ ሌላ ተመሳሳይ የሆነ ነገር መፈጸሟ አይቀርም የሚል ቃና ያለው አስተያየት ሲሰጥ ሁሉ ይደመጣል:: በእውነት በጣም የሚያሳዝን አስተያየት ነው:: በአንድ ውድድር ላይ በመዘናጋት መጠኑን የዘለለ ድርጊት የፈጸመች መምህርት እህታችን ( ለኔ ወሲብ መፈጸሟ ሙሉ በሙሉ እንደ ወንጀኛ  የሚያስቆጥራት ሳይሆን በመዘናጋት ትንሽ መጠኑን ያለፈና ባታደርገው ሁላችንም የምንመርጠው ድርጊት ነው) ምንም ማረጋጫ ሳይኖር ወደፊት በማንኛውም ጊዜና  የትም ቦታ  ይህንኑ የምታደርግ ተደርጎ  በሚድያ ከአንድ ጋዜጠኛ አስተያየት መስማት  እጅግ ያማል::


አለምነህ አስተያየቱን በመቀጠል ቤቲ ይህንን ድርጊት የፈጸመችበት የተለያዩ  በጣም ብዙ አሳሳችና አዘናጊ ምክንያቶች ሊኖሩ ስለሚችሉ ብዙም ሊፈረድባት እንደማይገባ ይገልጽና  መልሶ  ደግሞ  ቤቲ ለፍቅር ብላ ቢሆን እንደዚህ ያደረገችው እኔ አንገቴን ለቢላ  እሰጥላት ነበር ግን አይደለም ለገንዘብ ብላ ነው ይህን ሁሉ ያደረገችው ብሎ በአንድ ጊዜ ሁለት የሚጋጩና  ባልተረጋገጠ መላምት ላይ የተመሰረቱ አስተያየቶችን ያስደምጠናል::


አለምነህ በማጠቃለያው ቤቲ ውድድሩን አቋርጣ እንድትመለስም ይመክራል:: ይገርማል የውድድሩን ህግና  ስርአት ያላፋለሰች እና ምናልባትም ጠንክራ በውድድሩ ውስጥ ከቆየች የማሸነፍ ተስፋ ሊኖራት የሚችልን ተወዳዳሪ እኔ ማየት የማልፈልገውን ነገር በማድረጓ  ከውድድሩ መውጣት አለባት ብሎ  መፍረድ ምን አይነት ፍርድ እንደሆነ  ለአድማጭ እተወዋለሁ:: ሲሆን ሲሆን ስህተቶቿን እያስተካከለች ለማሸነፍ እንድትጣጣር መገፋፋት ይገባል እንጂ ወደ ኋላ  እንድታፈገፍግና  እንድትሸማቀቅ ማድረግ ተገቢ አይመስለኝም:: የሄደችውስ ከተሳካ አሸንፋ ለመመለስ እንጂ በትንሽ መዘናጋት በተፈጠረ ጉዳይ ተስፋ ቆርጣ ለመመለስ ነው እንዴ? አለምነህ ንግግሩን ሲያሳርግ ደግሞ ኢትዮጵያውያን ቆንጆዎች ናቸው ሲባል እንደ ቤቲ ማለት አይደለም ሲል የቤቲን ቁንጅና ከኢትዮጵያውያን ቁንጅና ለመለያየትም ጥረት ሲያደርግ ይታያል:: 

ያንተ ያለህ ጆሮ  መቼም አይሰማው የለም:: አይ አለምነህ የኢትዮጵያውያን ቁንጅና እንደ ቤቲ ካልሆነ ታድያ እንደማን ነው? እንዳንተ ይሆን? ለመሆኑ አንተ ያልጣመህን ወይንም ያልተመቸህን ነገር ያደረገ ሁሉ ኢትዮጵያዊ ቁንጅናው ይገፈፋል ማለት ነው? ለካስ ከጋዜጠኝነትህም በተጨማሪ ቁንጅና ሰጭና  ነሺም ሆነሃል? ቤቲማ ልቅም ያለች ኢትዮጵያዊት ቆንጆ  ናት በተለያዩ  ምክንያቶች በመዘናጋት በአንድ ውድድር ላይ ትንሽ መጠኑን ያለፈ ድርጊት የፈጸመ ግለሰብ ቁንጅናው ይነጠቃል የሚል ህግ ካለ እራሱ አልምነህ ያስረዳን::


ጋዜጠኛ አለምነህ ለመሆኑ ኢትዮጵያ የተዋረደችው በቤቲ የአጋጣሚ መጠኑ ያለፈ ድርጊት ነው እንዴ? ፍጹም በሆነ የአስተዳደር ብልሹነት፣ ፍትሃዊ ባልሆነ የሃብት ክፍፍልና  አምባገነናዊ አገዛዝ በሃገራቸው የመኖር ተስፋ አጥተው በሱዳን እና በ ሊብያ በረሃ የማንም አረብና ጥቁር መጫወቻ  ሰለሆኑት እህቶቻችን ምነው ዝም አልክ? አለም ደቻሳ በኢትዮ. ኢምባሲ በር ላይ በአረቦች ስትደበደብና ስትጎተት ለዚህ ሁሉ የዳረገንን የአስተዳደር ብልሹነት መሆኑን እያወቅክ ምነው ልሳንህን ያዘው? ዛሬ በአዲስ አበባ እና በተለያዩ ከተሞች የውጭ ዜጋ የሆነ ጥቁር ይሁን ነጭ እንዲሁም  ካገሬውም ሰው ቢሆን ትንሽ ገንዘብ ለማግኘት ለስጦታ እንደተዘጋጀ የገበያ እቃ ራሳቸውን አሳምረውና ተሽቀርቅረው ሰለሚቀርቡት በሺዎች ለሚቆጠሩ የእህቶቻችን ጉዳይስ  ዜናው አልደረሰህ ይሆን?   እዛው አፍንጫህ ስር በአለቆችህ ቀጭን ትእዛዝ ጋዜጣ ላይ ሃሳባቸውን ስለገለጹ ብቻ  በአሸባሪነት ተከሰው ወህኒ ስለተወረወሩት ስለ እነ እስክንድር ነጋ ፣ ርእዮት እና ሰለብዙ የግፍ እስረኞች ጉዳይስ ትንሸ  አቆጠቁጥህም?  ከእነዚህና  ከመሳሠሉት በላይስ ሃገራዊ ውርደት አለ? 


ለቤቲ ቤተሰቦች፣ ጓደኞች፣ ዘመዶችና ለመለው ህብረተሰባችን በሙሉ


ቤቲ አንዲት ኢትዮጵያዊ እህታችን በሃገራችን ያለውን ባህላዊ፣ ማህበረሰባዊ እና ስነልቦናዊ ጫናዎችን ተቋቁማ በዚህ መድረክ ላይ በመሳተፏ አድናቆት ይገባታል:: በመዘናጋት ትንሽ መጠኑ ከፍ ያለና ባታደርገው ሁላችንም የምንመርጠው ነገር ግን ሁሌም እኛ ባሰብነው ብቻ  ሳይሆን ባላሰብነው መንገድ ነገሮች ተከስተው ቤቲ ይህንን ነገር ብታደርግም ምንም ማለት ያልሆነና  ቀጣይ ቆይታዋ የተሳካ  ሆኖላት ጥሩ ውጤት እንድታመጣ ሁላችንም ከሆኗ ልንሆንላት ይገባል:: ወደድንም ጠላንም ቤቲ የኛው እህት፣ የኛው ልጃችን ናት:: እንደስህተትም ከተቆጠረባት የሚሰራ ሰው ይሳሳታልና ስህተቷን አስተካክላ ነገ  የተሻለ ስብእና እንዲኖራት ሁላችንም ከሆኗ እንሁን:: ስሜቷን ከሚጎዱ መንፈሷን ከሚረብሹ ድርጊቶች ተቆጥበን በሰላም ተቀብለን የቀድሞ ህይወቷን ምንም ባለመሳቀቅ እንድትቀጥል እንርዳት እላለሁ ::



አመሰግናለሁ::

የምልህ አለኝ የሚለኝ ካለ ይሄው መገኛዬ…. fasil_ayal@yahoo.com

No comments:

Post a Comment