Tuesday 1 January 2013

ኦሮሚያ ዉስጥ ዳኞች በብዛት ስራቸዉን እየለቀቁ መሆኑ ተነገረ

ኦሮሚያ ክልል ዉስጥ በተለያየ ደረጃ በዳኝነት ስራ ላይ የተሰማሩ ዜጎች ስራችንን ከፖለቲካ ተጽእኖ ነጻ በሆነ መንገድ ለመስራት አልቻልንም በሚል በብዛት ስራቸዉን እየለቀቁ መሆኑን ከወደ አሮሚያ የሚደርሱን ዜናዎች ያስረዳሉ። ባለፉት ሁለት አመታት ብቻ ዘረኛዉ የወያኔ አገዛዝ በዳኝነት ስራ ላይ የሚያደርገዉን የፖለቲካ ጣልቃ ገብነት በመቃወም ከ100 በላይ ዳኞች ስራቸውን የለቀቁ ሲሆን በያዝነው አመት ደግሞ ይሀ ቁጥሩ በእጥፍ ሊጨምር እንደሚችል በኦሮሚያ ክልል የሚገኙ ዘጋቢዎቻችን በላኩልን ዜና ገለጹ።


ከአንድ ወር በፊት የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንትና ምክትል ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩት አቶ ታደለ ነጊሾና አቶ ሰይድ ጁንዲን ስልጣናቸውን ህጋዊ ባልሆነ መንገድ እንዲለቁ ከተደረጉ በሁዋላ፣ ችግሩ መባባሱ ተገልጾአል።ሁለቱ ፕሬዚዳንቶች አሁን ባለው የፌደራል ስርአትና በክልሉ መንግስት ላይ አመኔታ ስለሌላቸው ከስልጣን እንዲለቁ መደረጋቸውን ስማቸው እንዳይገለጥ የፈለጉ ዳኞች ለኢሳት ተናግረዋል።

የኦሮሚያ ምክር ቤት አዋጅ ቁጥር140/99 መሠረት ፕሬዚዳንቱና ምክትላቸዉ ከስልጣን የሚወርዱት በፈቃድ፣ በህመም ፣ በጡረታ ወይም ቅሬታ ካለ ቅሬታው ለምክር ቤቱ አፈ ጉባኤ ቀርቦ አስፈላጊው ማጣራት ከተደረገ በሁዋላ መሆኑን ቢደነግግም፣ በቅርቡ ስልጣናቸዉን ያጡት አቶ ታደለና አቶ ሰይድ ከስልጣን እንዲወርዱ የተደረገበት አካሄድ ግን የክልሉ ምክር ቤት አዋጅ ከሚደመግገዉ ዉጭ መሆኑ ታዉቋል። አቶ ታደሰን በህገወጥ መንገድ ተክቶ የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ሆኖ የተሾመዉ ግለሰብ  በኦህዴድ አመራር አባልነቱ የሚታወቅና ከገዢውን ፓርቲ  ከህወሀት/ኢሀዴግ ጋር የቅርብ ትስስር ያለዉ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል።

አንድ ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የጠየቁን የከፍተኛዉ ፍርድ ቤት ዳኛ በስልክ አንደተናገሩት የአዲሱ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ሹመት  “ህዝብን መናቅና ህዝብ ምን ያመጣል” በሚል ንቅት የተደረገ  መት መሆኑንና  “ትናንት ድርጅቴ ኢህአዴግ እንዲህ አድርጎአል እያሉ በሚዲያ ሲናገሩ የነበሩ ሰው ዛሬ ፍትሀዊ ዳኝነት ይሰጣሉ ብሎ ማሰብ አይቻልም” በማለት ዳኞች ሃላፊነታቸውን እየለቀቁ ከመሄድ ውጭ ሌላ አማራጭ እንደሌላቸዉ አስረድተዋል።

No comments:

Post a Comment