Wednesday 16 January 2013

ቅዱስ ሲኖዶስ ያካሄደው ስብሰባ ውጥረት የተሞላበትና የመንግስት ግልጽ ጫና የታየበት መሆኑን የቤተክህነት ምንጮች ገልፁ

ጥር ፯ (ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሀዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በአዲስ አበባ በትናንትናው እለት ያካሄደው ስብሰባ ውጥረት የተሞላበትና የመንግስት ግልጽ ጫና የታየበት መሆኑን የቤተክህነት ምንጮች ገልጸዋል::

መንግስትም አቡነ መርቆሪዎስ መንበራቸው ላይ ተመልሰው ማየት እንደማይፈልግ በአቶ አባይ ጸሀዬ በኩል ግልጽ አቆሙን ያንጸባረቀ በመሆኑ የዕርቁ ጉዳይ ፍጻሜ ላይ መድረሱን ለማወቅ ተችሎል::

በውጭ የሚገኙ አባቶች በዛሬው እለት በሎስ አንጀለስ በጀመሩት የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ላይ ለመገኘት ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሪዎስ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘ ኢትዮጵያ በትላንትናው እለት ከካናዳ ሎስአንጀለስ ገብተዋል::


ትላንት በአዲስ አበባ በተካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ላይ ለተገኙት አባቶች አቶ አባይ ጸሀዬ በግልጽ እንዳስታወቁት አቡነ መርቆሪዮስ ወደ መንበራቸው ይመለሱ ማለት መንግስቱ ሀይለማሪያም ይመለስ ከማለት ተለይቶ አይታይም ማለታቸው ተሰምቶል::

መንግስት አቡነ መርቆሪዎስ ቢመለሱ ግድ እንደሌለው ነገር ግን ፓትሪያርክ ሆነው ማየት እንደምይፈልግ አቶ አባይ ጸሀዬ አረጋግጠዋል::

ስለሆነም የ 6 ኛውን የፓትርያርክ ምርጫ ሂደት እንዲያፋጥኑ እንዳሳሰቦቸውም መረዳት ተችሎል::

አንዳንድ ከመንግስት ጋር የሚሰሩ ጳጳሳት በተለይም ብጹዕ አቡነ መቃሪዮስ አቡነ መርቆሪዮስ የሚመለሱ ከሆነ እኛም አክሱም ላይ የራሳችን ሲኖዶስ እናቆቁማለን በማለት ቤተክርስቲያኒቱን በግልጽ በዘር መስመር ለማስቀመጥ ሀሳብ መሰንዘራቸውን የተገኘው ዜና ያብራራል::

ዕርቁን የሚደግፉና አቡነ መርቆሪዎስን በመንበር ማየት የሚፈልጉ ጳጳሳት ቁጥር እየጨመረ የመጣ ቢሆንም መንግስት አቆሙን በግልጽ ማስቀመጡን ተከትሎ የመንግስት ፍላጎት ባገናዘበ መልኩ ስብሰባው እንዲጠናቀቅ እየተጠበቀ ነው::

No comments:

Post a Comment